በኮሎምቢያ ዩኒቨርስቲ ውስጥ ድንኳኖችን የዘረጉት የፍልስጤም ደጋፊዎች በተቃውሟችን እንቀጥላለን አሉ

በኮሎምቢያ ዩኒቨርስቲ ግቢ ውስጥ ለአንድ ሳምንት ያህል ድንኳኖችን ተክለው በፍልስጤማውያን ላይ እየደረሰ ያለውን ጥቃት እየተቃወሙ ያሉ ተማሪዎች በተቃውሟቸው እንደሚቀጥሉ ተናገሩ።

የኮሎምቢያ ዩኒቨርስቲ ፕሬዚዳንት ተማሪዎቹ ከግቢው እንዲወጡ ቀነ ገደብ ቢያስቀምጡም በተማሪዎች ዘንድ ተሰሚነት አላገኙም።

ዶክተር ሚኖውቼ ሻፊክ ድንኳኖችን ዘርግተው እየተቃወሙ ያሉትን ተማሪዎች በኒውዮርክ ከተማ ከሚገኘው የዩኒቨርስቲው ግቢ ለቀው የማይወጡ ከሆነ እና ስምምነት ላይ መደረስ ካልተቻለ “አማራጭ እርምጃዎችን” ሊወሰድ እንደሚችል አስጠንቅቀዋል።

የፍልስጤም ደጋፊዎችን የወከለው ቡድን በበኩሉ ከዩኒቨርስቲው ባለስልጣናት ጋር በሚደረገው ድርድር እንደማይቀጥል አስታውቀዋል።

የፍልስጤም ደጋፊ ተማሪዎች እስራኤል በጋዛ ላይ የምታደርገውን የዘር ጭፍጨፋ በጦር መሳሪያ እና በሌሎች ነገሮች እያገዙ ነው ካሏቸው ኩባንያዎችም ጋር የንግድ ሽርክናቸውን ዩኒቨርስቲዎች እንዲያቆሙ እየጠየቁ ይገኛሉ። እስራኤል በጋዛ በሚገኙ ፍልስጤማውያን ላይ የዘር ጭፍጨፋ እየፈጸመች ነው የሚለውን አትቀበለውም።

ከዚህም ጋር በተያያዘ የአሜሪካ የተወካዮች ምክር ቤት አፈ ጉባዔ ማይክ ጆንሰን በኮሎምቢያ ዩኒቨርስቲ ተቃዋሚዎች ንግግር ማቋረጥን ጨምሮ ከፍተኛ ተቃውሞ ገጥሟቸዋል።

“ድምጽዎት አይሰማም” የሚሉ እና ሌሎችንም ንግግሮችን በመጮህ እንዳይሰሙ አድርገዋቸዋል።

አፈጉባኤው የኮሎምቢያ ዩኒቨርስቲ ባለስልጣናት ሁኔታውን መቆጣጠር ተስኗቸዋል ከማለት በተጨማሪም የዩኒቨርስቲው ፕሬዚዳንት ሻፊቅ እንዲወርዱ ጠይቀዋል።

በኮሎምቢያ የፍልስጤም ደጋፊ ተማሪዎች ፖሊስ በተቃዋሚዎቹ ላይ እየወሰደ ያለውን እርምጃ በመፍቀዳቸው ከስልጣን እንዲለቁ ጠይቀዋል። በኮሎምቢያ ዩኒቨርስቲ ሰኞ በነበረው ተቃውሞ 133 ተማሪዎች ታስረዋል።

በመላው አሜሪካ ባሉ ዩኒቨርስቲዎች የፍልስጤም ድጋፎች እየተቀጣጠሉ እና በግቢዎቻቸው ውስጥ ድንኳን አድረው ሌት ተቀን የሚቃወሙ ተማሪዎች እየታዩ ይገኛሉ። ከዚህም ጋር ተያይዞ በያሊ እና በሌሎችም ዩኒቨርስቲዎች የፍልስጤም ደጋፊ ተማሪዎች ታስረዋል። አንድ ዩኒቨርስቲም በድጋፍ ሰልፉ የተነሳ ሲዘጋ ስመ ጥሩው ሃርቫርድ ዩኒቨርስቲ ወደ ግቢው መግባት ላይ ገደብ ጥሏል።

የኮሎምቢያ ዩኒቨርስቲ ባለስልጣናት በተቋሙ ግቢ ውስጥ ድንኳን ዘርግቶ መቃወም የዩኒቨርስቲውን ደንብ የጣሰ ነው ብለዋል።

እስራኤል በከበባ ውስጥ ባስገባቻት ጋዛ ውስጥ የጀመረችውን የተቀናጀ ጥቃት ተከትሎ ከ34 ሺህ 180 በላይ ፍልስጤማውያን መገደላቸውን ከጋዛ የጤና ሚኒስቴር የተገኘው መረጃ ያስረዳል። ከነዚህም ውስጥ አብዛኛዎቹ ሴቶች እና ህጻናት መሆናቸውም በሐማስ አስተዳደር ስር ካለው የጤና ሚኒስቴር የተገኘው መረጃ ያስረዳል።

ሐማስ መስከረም መጨረሻ ላይ በደቡብ እስራኤል በፈጸመው ጥቃት 1 ሺህ 200 ሰዎች መገደላቸውን እና 253 ታጋቾች መወሰዳቸውን የእስራኤል ባለስልጣናት ማስታወቃቸው ይታወሳል።

በድህረ ገጻችን ኢትዮ አማዞን በመግባት የሚፈልጉትን እቃ ማዘዝ  ብቻ  ሳይሆን የርስዎንም እቃዎች መሸጥ እንደሚችሉ ስናሳውቅዎት በደስታ ነው ። ለማስታወቂያ ወይንም ለመግቢያ ምንም ክፍያ አይጠበቅብዎትም፤  ለተጨማሪ መረጃ   ድህረ ገጻችንን ይጎብኙ። https://ethio-amazon.com/

ለበለጠ መረጃ ሊንኩን በመንካት የቴሌግራም ግሩፓችንን ይቀላቀሉ!https://t.me/ethioamazon

ምንጭ ( ቢቢሲ ዜና )