“ … ለኩራዝ የሚጠቀሙበት ነዳጅ በግልጽ ሁኔታ በችርቻሮ፣ የአረቄ በርሜል በከፍተኛ መጠን የሚሸጥበት ቦታ ነው ” – አቶ ንጋቱ ማሞ

በአዲስ አበባ አቃቂ ቃሊቲ ክፍለ ከተማ አቃቂ ገበያ ማዕከል ትላንት ከምሽቱ 3 ሰዓት ገደማ የእሳት አደጋ አጋጥሞ ነበር።

በሰዎች ላይ ጉዳት ያልደረሰ ሲሆን 6 ሙሉ ለሙሉ፣ 10 በከፊል፣ በድምሩ 16 ሱቆች እንደተቃጠሉ የአዲስ አበባ ከተማ እሳትና አደጋ ሥራ አመራር ኮሚሽን ለቲክቫህ ኢትዮጵያ ገልጿል።

የአደጋው መንስኤ ታውቋል? ተብሎ ለቀረበላቸው ጥያቄ በሰጡት ምላሽ የኮሚሽኑ የሕዝብ ግንኙነት ባለሙያ አቶ ንጋቱ ማሞ፣ “ ፓሊስ ምርመራ እያደረገ ነው። በንብረት ላይ የደረሰን ጉዳትም ባለንብረቶቹን ፓሊስ አጣርቶ ምርመራ እያደረገ ነው ” ብለዋል።

ገበያ ማዕከሉ ለእሳት አደጋ ተጋላጭ ተብሎ የተለዬ እንደሆነ ፣ ለአደጋ የተጋለጠባቸውን ጉዳዮች ለሚመለከታቸው አካላት ቢያቀርብም የማስተካከያ እንዳልተደረገ ኮሚሽኑ ያስታወቀ ሲሆን፣ ቲክቫህ ኢትዮጵያም ተሰጥቶ የነበረው ማስጠንቀቂያ ምን እንደነበር ኮሚሽኑን ጠይቋል።

አቶ ንጋቱ በሰጡት ምላሽ፣ “ ለገበያ ማዕከሉ አክሲዮን ማኅበራት አደጋ ውስጥ ናችሁ። ገበያ ማዕከሉ በዘመናዊ መልክ ይገንባ ንብረታችሁ ለአደጋ ሰለባ እንዳይሆን የሚል ምክረ ሀሳብ አቅርበናል። በግልባጭ ደግሞ ለወረዳውም ” ብለዋል።

“ ቤቶቹ በቀላሉ ሊቀጣጠሉ ከሚችሉ ግብዓቶች (ቆርቆሮ በቆርቆሮ) የተገነቡ ናቸው። መፍትሄ ብለን ያቀረብነው ገበያ ማዕከሉ ዘመናዊ ሆኖ እንዲገነባ ነው። ዘመናዊ ስንል እሳትን ሊቋቋም ከሚችል እንደ ድንጋይ ከመሳሰሉ ግብዓቶች እንዲሰራ ነው ” ሲሉ አስረድተዋል።

አቶ ንጋቱ፣ “ ከገጠር የሚመጡ ሰዎች ለኩራዝ የሚጠቀሙበት ነዳጅ በግልጽ በችርቻሮ፣ የአረቄ በርሜል በከፍተኛ መጠን የሚሸጥበት ቦታ ነው” ብለዋል።

“ ንግዱ ዘርፍ፤ ዘርፍ ያስፈልገዋል። በጎን ከፍተኛ ዋጋ ያላቸው የኤሌክትሮኒክስ እቃዎች እየተሸጡ፣ በጎን ደግሞ የካቲካላ ንግድ በፍጹም ምንም አይነት ህብረት የላቸውም ” ነው ያሉት።

የገበያ ማዕከሉ በተደጋጋሚ አደጋ እንደደረሰበት አስታውሰው፣ አደጋ ቢያጋጥም እንኳ የአደጋ መቆጣጠር ተሽከርካሪ ለማስገባት ምቹ ባለመሆኑ፣ በውስጡ የሚከናወኑ የንግድ ዘርፎች የተደበላለቁ በመሆናቸው የሚመለከታቸው አካላት አሁንም ትኩረት እንዲሰጡ አሳስበዋል።

በድህረ ገጻችን ኢትዮ አማዞን በመግባት የሚፈልጉትን እቃ ማዘዝ  ብቻ  ሳይሆን የርስዎንም እቃዎች መሸጥ እንደሚችሉ ስናሳውቅዎት በደስታ ነው ። ለማስታወቂያ ወይንም ለመግቢያ ምንም ክፍያ አይጠበቅብዎትም፤  ለተጨማሪ መረጃ   ድህረ ገጻችንን ይጎብኙ። https://ethio-amazon.com/

ለበለጠ መረጃ ሊንኩን በመንካት የቴሌግራም ግሩፓችንን ይቀላቀሉ!https://t.me/ethioamazon

ምንጭ(@tikvahethiopia)