ፎረስት የተፎካካሪ ቡድን ደጋፊ የሆኑት የቫር ዳኛ ሦስት ፍጹም ቅጣት ምቶች ከለከሉኝ አለ

በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ ላለመውረድ እየታገለ የሚገኘው ኖቲንግሃም ፎረስት የተፎካካሪ ቡድን ደጋፊ የሆኑት የቫር ዳኛ ሦስት ፍጹም ቅጣት ምት ከለከሉኝ አለ።

ፎረስት ይህን ያለው ትናንት ሚያዚያ 14/2016 ዓ.ም. በሊጉ ሌላ የመውረድ ስጋት ካለበት ኤቨርተን ጋር ባደረው ጨዋታ 2 ለ 0 ከተሸነፈ በኋላ ነው።

እሁድ ዕለት በነበረው ጨዋታ የመሃል ዳኛው እና የቪዲዮ ረዳት ዳኛው ለፎረስት ፍጹም ቅጣት ምት የመከልከላቸው ጉዳይ ብዙ አነጋግሯል።

ፎረስት ከጨዋታው በኋላ ለሽንፈቱ ምክንያት ያለውን “እጅግ በጣም ደካማ ዳኝነት” በተመለከተ “የራሱን አማራጭ እንደሚወስድ” ባወጣው መግለጫ አስታውቋል።

ክለቡ ከጨዋታው በፊት የቫር ዳኛው በሊጉ ላለመውረድ እየታገለ የሚገኘው የሉተን ደጋፊ መሆናቸውን በመግለጽ የዳኛ ለውጥ እንዲደረግ መጠየቁን ገልጿል።

ይሁን እንጂ ለጥያቄ የዳኞች ቦርድ መልስ ሳይሰጥና ዳኛው ሳይቀየሩ ጨዋታው መከናወኑን ፎረስት ገልጿል።

ፎረስት በመግለጫው የቫር ዳኛውን ስም በይፋ ባይገልጹም የዕለቱ የቫር ዳኛ ስቱአርት አትዌል ነበሩ።

“ትዕግስታችን በተደጋጋሚ ተፈትኗል” ይላል ክለቡ በተደጋጋሚ በዳኛ ውሳኔ ሳይስማማ መቅረቱን ለመግለጽ ባወጣው መግለጫ።

ከትናንቱ ጨዋታ በኋላ ፎረስት ከወራጅ ቀጠና አንድ ደረጃ ከፍ ብሎ በ26 ነጥብ 17ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ኤቨርተን ትናንት ያገኘውን ድል ተከትሎ ነጥቡን 30 አድርሶ 16ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። ሉተን ደግሞ በ25 ነጥብ ከፎረስት አንድ ደረጃ ዝቅ ብሎ 18ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል።

ከጨዋታው በኋላ የፎረስት አሰልጣኝ ኑኖ እስፒሪቶ ሳንቶስ ዳኝነቱን በተመለከተ በሰጡት አስተያየት “የክለቡን ስሜት እጋራለሁ በዚህ ጨዋታ ብቻ ሳይሆን እኛን የጎዱ የዳኝነት ውሳኔዎች ሲተላለፉብን ነበር። በዳኞች ውሳኔ ደስተኞች አይደለንም” ብለዋል።

ቢቢሲ የዳኞች ማሕበርን አስተያየት ጠይቆ ምላሽ አላገኝም ይሁን እንጂ ምንጮች የእግር ኳስ ማኅበር የተሰጡ የዳኝነት ውሳኔዎችን እየመረመረ እንደሚገኝ ጠቁመዋል።

ፎረስትን ያጋጠመው ምን ነበር?

ፎረስት ይገባን ነበር ላሉት ፍጹም ቅጣት ምቶች ጥፋት ፈጽሟል የተባለው የቀድሞ የማንቸስተር ዩናይትድ ተጫዋች አሽሊ ያንግ ነው።

በመጀመሪያው አጋማሽ ሁለቱም ክለቦች 0 ለ 0 በነበሩበት ወቅት ያንግ ፍጹም ቅጣት ምት ክልል ውስጥ ኳስን ለመምታት ሲል የፎረስት አጥቂን እግር መትቶ ነበር።

የመጀመሪያው አጋማሽ ማብቂያ ላይ ደግሞ ካለም ሀድሰን-ኦዶይ ያሻማት ኳስ የአሽሊ ያንግን እጅ ገጭታ ወደ ውጪ ወጥታለች።

ሦስተኛው ክስተት ደግሞ በሁለተኛው አጋማሽ ኤቨርተን 1 ለ 0 እየመራ ሳለ ያንግ የፍጹም ቅጣት ምት ሳጥን ውስጥ ሀድሰን-ኦዶይን ጠልፎ ቢጥልም የመሃል ዳኛው አንተኒ ቴይለርም ሆኑ የቫር ዳኛው ስቱአርት አትዌል ጣልቃ ሳይገቡ ቀርተዋል።

“ይሄን አምኖ መቀበል በጣም ከባድ ነው። ጊዮ ተጠልፏል። ከዛ ኳስ በግልጽ በእጅ ተነክቷል። እንደገና ሀድሰን-ኦዶይን ያጋጠመው ክስተት አለ። . . . መጥፎ ዳኝነትን አንፈልግም” ሲሉ አሰልጣኝ ሳንቶስ ተናግረዋል።

በድህረ ገጻችን ኢትዮ አማዞን በመግባት የሚፈልጉትን እቃ ማዘዝ  ብቻ  ሳይሆን የርስዎንም እቃዎች መሸጥ እንደሚችሉ ስናሳውቅዎት በደስታ ነው ። ለማስታወቂያ ወይንም ለመግቢያ ምንም ክፍያ አይጠበቅብዎትም፤  ለተጨማሪ መረጃ   ድህረ ገጻችንን ይጎብኙ። https://ethio-amazon.com/

ለበለጠ መረጃ ሊንኩን በመንካት የቴሌግራም ግሩፓችንን ይቀላቀሉ!https://t.me/ethioamazon

ምንጭ ( ቢቢሲ ዜና )