የማንቸስተር ዩናይትድ ሽንፈት ጠባሳ እና የካሰሚሮ ጉዳይ

ማንቸስተር ዩናይትድን አስበው ከዚህ የባሰ መጥፎ ጊዜ የለም ሲሉ ከድጡ ወደ ማጡ መሆኑን አሳየ።

በርካታ መጥፎ ክብረ ወሰኖችን እያስመዘገቡ ባሉበት ዓመት ዩናይትዶች ከሰኞ ምሽቱ የክሪስታል ፓላስ ሽንፈት በኋላ በአውሮፓ መድረክ የመወዳደራቸው ጉዳይ እያበቃለት ይመስላል።

ሽንፈቱ ቡድኑን በስምንተኛ ደረጃ ላይ አስቀምጦታል።

ወደ አውሮፓ ውድድር ለማለፍ ከማንቸስተር ሲቲ ጋር ያለባቸውን የኤፍኤ ዋንጫ ማሸነፍ ሌላኛው አማራጭ ነው።

10 የዋናው ቡድን ተጫዋቾች ቢጎዱም አሰልጣኙ ቴን ሃግ ቡድኑን ለማዳራጀት አልቻሉም።

“ግልጽ ነው። ከደረጃ በታች ነው የተጫወጥነው” ብለዋል ከፓላሱ ሽንፈት መልስ።

“ማድረግ የሚጠበቅብንን አላደረግንም። በሚገባን ደረጃ አልነበርንም” ሲሉ አክለዋል።

የሽንፈቱ ጠባሳዎች

  • 13ኛ ሽንፈት ሲሆን በአንድ ውድድር ዘመን ያስመዘገቡት የሽንፈት መጠን ነው።
  • ቡድኑ በሊጉ ከሰባተኛ ደረጃ በታች ሆኖ ጨርሶ አያውቅም።
  • ከሜዳቸው ውጭ በአራት ጎል ልዩነት በመሸነፍ ከኖቲንግሃም ፎረስት ቀጥለው ሁለተኛ ቡድን ሆነዋል።
  • የፓላሱ ሽንፈት የውድድር ዓመቱ ትልቁ ሽንፈት ነው።
  • ከ1976-77 ወዲህ 81 ጎሎችን አስተናግደዋል። ይህም በርካታ ጎሎችን ያስተናገዱበት ሆኗል።

ቴን ሃግ ውላቸው ሊጠናቀቅ አንድ ዓመት ቢቀረውም በኃላፊነት የመቆየታቸው ነገር ጥያቄ ውስጥ ከገባ ወራት ተቆጥረዋል።

ካለፉት 11 ጨዋታዎች 10 ነጥብ ብቻ ነው ያሳኩት።

ከእነዚህ ጨዋታዎች መካከል በፉልሃም፣ በብሬንትፎርድ፣ ቼልሲ፣ ሊቨርፑል እና በርንሌይ ባለቁ ደቂቃዎች በተቆጠሩባቸው ጎሎች 10 ነጥቦችን አጥተዋል።

ቴን ሃግ በአስልጣኝነት ዘመናቸው አይተውት የማያውቁትን የጉዳት መጠን ማስተናገዳቸውን ተናግረዋል።

ከፓላስ ጋር በተከላካይ ቦታ ላይ የተሰለፉት የ32 ዓመቱ ካሰሚሮ እና የ36 ዓመቱ ኤቫንስ 14ኛ የተከላካይ ጥምረታቸው ነው።

በቅርቡ የክለቡን ድርሻ የገዙት ሰር ጂም ራትክሊፍ በአሰልጣኙ ዙሪያ ውሳኔያቸውን እንዲያሳውቁ ጫናው በርትቶባቸዋል።

የቀድሞው የሊቨርፑል ተከላካይ ጂሚ ካራገር ለአሰልጣኙ ብዙም ያዘነ አይመስልም።

“ይህ በፕሪሚየር ሊጉ በደንብ ያልሰለጠነው ቡድን መሆኑ ግልጽ ነው። ቴን ሃግ ውጤት ይፈልጋል” ብሏል።

“አንድ ነገር ስለመኖሩ ሊያሳምነን ይገባል። የማንቸስተር ከ23 ዓመት በታች ቡድን በዚህ መልኩ እንደማይሸፈን አስባለሁ። በበርካታ ታላላቅ አሰልጣኞች እንደመሰልጠኔ አንድም ነገር ግን በዚህ ቡድን ላይ አልመለከትም።”

የቀድሞው የማንቸስተር ዩናይትድ የአሁኑ የኤቨርተን ተከላካይ አሽሊ ያንግ በበኩሉ “የዛሬውን አይነት እንቅስቃሴ ከደገሙት ከአውሮፓ ውድድር ውጭ ይሆናሉ” ብሏል።

“ለመሮጥ እንኳን ፈቃደኛ ካልሆኑ አደጋ ውስጥ ይገባሉ። ዘንድሮ ወደ ላይ ወደ ታች ሲሉ ቆይተዋል። በዚህ ጨዋታ ግን ብዙዎቹ ተጫዋቾች በጥሩ ብቃት ላይ አልነበሩም። ፓላሶች የአዋቂዎች እና የታዳጊዎች ጨዋታ እንዲመስል አድርገውታል።” ሲል ተችቷል።

‘ተገቢ ሽንፈት’

ባሳዩት እንቅስቃሴ ባይሆንም ማንቸስተር ዩናይትድ ተጫዋቾች ከጨዋታው መጠናቀቅ በኋላ በደጋፊዎቻቸው ተጨብጭቦላቸው ከሜዳ ወጥተዋል።

“እንደ ማንቸስተር ከዚህ በላይ መንቀሳቀስ ነበረብን። የነበሩት ተጫዋቾች ከዚህ በላይ መስራት ነበረባቸው። ተገቢ ሽንፈት ነው። የጠበቅነው እንቅስቃሴ አይደለም” ሲሉ ቴን ሃግ ለቢቢሲ ተናግረዋል።

“በቡድኑ እንቅስቃሴ ላይ ማተኮር አለብን። ይህ ተገቢ አይደለም። ለእሑድ ማስተካከከል ይኖርብናል። ከዚህ ጨዋታ ተምረን ማስተካከል አለብን።”

የቴን ሃግ ቆይታ ባጠራጠረበት በዚህ ወቅት እሑድ ዕለት ማንቸስተር ዩናይትድ አርሰናልን ይገጥማል። ቡድኑን ለመምራት ተገቢው ሰው ስለመሆናቸው በስካይ ስፖርት የተጠየቁት ቴን ሃግ “በትክክል” ሲሉ መልሰዋል።

“መልፋት ይጠበቅብኛል። ተገቢ ባለመሆኑ በተቻለኝ አቅም በሙሉ ቡድኑን ለማዘጋጀት መሞከር ይጠበቅብኛል” ብለዋል።

“ለዚህ ኃላፊነት መውሰድ ይኖርብኛል። ለእሑዱ ጨዋታም ላዘጋጃቸው ጉልበቱ ይኖረኛል።”

“ዓመቱን በሙሉ በርካታ ችግሮች ነበሩብን። ችግሮች ሲገጥሙን ለመፍታት ሞክረናል። ዛሬ ግን አላደረግነውም” ብለዋል።

‘እግር ኳስ ካሰሚሮ ተለያይታለች’

በጉዳት የሳሳውን የተከላካይ ክፍል ለመሸፈን የገባው ካሰሚሮ መጥፎ የሚባል ምሽት አሳልፏል።

የፖላሶቹ ኤበረቺ ኤዜ እና ማይክል ኦሊሴ ድንቅ ምሽት ባሳለፉበት ጨዋታ የቀድሞው ሪያል ማድሪድ አማካይ በተደጋጋሚ ተበልጦ ታይቷል።

የፓላስ ተጫዋቾች ስምንት ጊዜ ኳስ ይዘው አልፈውታል። ይህ ደግሞ በዘንድሮው ውድድር ዓመት በአንድ ጨዋታ የተመዘገበ ትልቁ ቁጥር ነው።

ባለፈው ዓመት ድንቅ ውድድር ዘመን ያሳለፈው ካሰሚሮ ዘንድሮ ብቃቱ ወርዷል።

“ካሰሚሮ በዚህ ጨዋታ ሊያውቅ የሚገባው ነገር በትልቅ ደረጃ እየተጫወተ ሊቀጥል የሚችለው ለሦስት ጨዋታ ብቻ መሆኑን ማወቅ አለበት። ቀሪዎቹን ሁለት የሊግ ጨዋታ እና ኤፍ ኤ ዋንጫውን ካከናወነ በኋላ ወደ አሜሪካ ወይንም ወደ ሳዑዲ መሄድ ይኖርበታል” ሲል ካራገር ተናግሯል።

“’እግር ኳስ ሳትለይህ ቀድመህ ተለያት’ እንደሚባል ሁሌም አስታውሳለሁ። እሱን እግር ኳስ ተለያይተዋለች። በከፍተኛ ደረጃ መጫወቱን አቁሞ ወደ ቀጣዩ ማለፍ አለበት” ብሏል።

“በእሱ ደረጃ የሚገኝ ተጫዋች በዚህ ውስጥ ማለፍ የለበትም። በክሪስታል ፓላስ መጫወቻ ሊሆን የማይገባው ትልቅ ተጫዋች ነው። አሁን ይበቃል ሊል ይገባል” ሲል አክሏል።

በድህረ ገጻችን ኢትዮ አማዞን በመግባት የሚፈልጉትን እቃ ማዘዝ  ብቻ  ሳይሆን የርስዎንም እቃዎች መሸጥ እንደሚችሉ ስናሳውቅዎት በደስታ ነው ። ለማስታወቂያ ወይንም ለመግቢያ ምንም ክፍያ አይጠበቅብዎትም፤  ለተጨማሪ መረጃ   ድህረ ገጻችንን ይጎብኙ። https://ethio-amazon.com/

ለበለጠ መረጃ ሊንኩን በመንካት የቴሌግራም ግሩፓችንን ይቀላቀሉ!https://t.me/ethioamazon

ምንጭ ( ቢቢሲ ዜና )